Return to BahaiPrayers.net
Facebook
ጌታ አምላኬ ሆይ፣ ስምህ የተወደሰ ይሁን! ጨለማ እያንዳንዱን ነገር ሸፍኗል፡፡ የክፋት ኃይሎችም የሁሉንም አገር ሕዝቦች ከበዋል፤ ይሁን እንጂ በእነዚህ ውስጥ የጥበብህን ውበቶች አያለሁ የአምላካዊ ጥበቃህንም ብርሃኖች ድምቀት እለያለሁ፡፡
እነዚያ ልክ በግርዶሽ የተሸፈኑ ያህል ከአንተ የተዘጉት፣ የአንተን ብርሃን ለማጥፋት፣ እሳትህን ለማዳፋን ፣ የፀጋህም ነፋሶች እንዳይነፍሱ ለመገደብ ኃይል አለን በለው ያስባሉ፤ አይቻላቸውም ፣ ለዚሁም የአንተ ታላቅነት ይመሰክርልኛል! እያንዳንዱ መከራ የጥበብህ ማህደር፣ እያንዳንዱም ስቃይ የአምላካዊ ጥበቃህ መጓጓዣ ስለሆነ እንጂ፣ የምድርና የሰማይ ኃይሎች ሁሉ ቢያብሩብንም እንኳ፣ ማንም ደፍሮ ባልተቃወመን ነበር፤ በፊቴ በግልጽ የተዘረጉትን የጥበብህን ድንቅ ምስጢራት ሁሉ ብገልጽ ኖሮ፣ የጠላቶችህ ልጓም ዛቦች በተበጣጠሱ ነበር፡፡
ስለዚህ አምላኬ ሆይ ፣ ምስጋና ለአንተ ይሁን! እነዚያን የሚወዱህን ከፈቃድህና ከበጎ ፍላጎትህ በሚጎርፈው ሕግ ዙሪያ እንድትሰበስባቸው፤ ለልቦቻቸውም እርግጠኝነትን የሚሰጠውን እንድትልክላቸው፤ ከሁሉም በላይ ታላቅ በሆነው ስምህ እማጸንሃለሁ፡፡ አንተ የሚያስደስትህን ሁሉ ለማድረግ የማይሳንህ ነህ፣ በእውነቱ አንተ በአደጋ ጊዜ ረዳቱ፣ በገዛ ራሱም ነዋሪው ነህ፡፡
አምላኬ ሆይ፣የቀናት ንጉስ የሆነውን ቀን፣ አንተ ከሁሉ በላቁት መልእክቶችህ ውስጥ ለሕሩያንህና ለነቢያትህ የተስፋ ቃል ያበሰርክለትን ቀን፣ የስሞችህን ሁሉ ክብር ውበት በተፈጠሩት ነገሮች ሁሉ ላይ ያበራህበትን ቀን ስለገለጽህ ስምህ የተመሰገነ ይሁን፤ ወደ አንተ የተመለሰ፣ አንተ ወዳለህበት የገባ የድምጽህንም ዜማዎች የሰማ ቡራኬው ታላቅ ነው፡፡
ጌታዬ ሆይ ፣ የግልፀትህ የላቁ ሐሴቶች የምድርህን ነዋሪዎች ሁሉ ነፍሶች ይሞሉ ዘንድ፤
እነዚያ ለአንተ ውድ የሆኑት ቃልህን በአገልጋዮችህ መካከል እንዲያወድሱ፣ ምስጋናህንም በፍጡራንህ መካከል እንዲያሰራጩ እንድትረዳቸው፣ በእርሱ የስሞችህ መንግስት በማምለክ በሚከበረው ስም እማፀንሃለሁ፡፡ ጌታዬ ሆይ ወደ ፀጋህ የህይወት ውሃዎች ስለመራሃቸው በችሮታህ ከአንተ እንዳይከለከሉ ፈቃድህ ይሁን፣ ወደ ዙፋንህም መኖሪያ ስለጠራሃቸው፣ በፍቅራዊ ደግነትህ፣ ከቅርበትህ እንዳታባርራቸው እለምንሃለሁ፤ ከአንተ በስተቀር ከማንኛውም ነገር ሙሉ በሙሉ እንዲላቀቁ የሚያደርጋቸውን ላክላቸው፤ የጨቋኞች ማየልም ሆነ፣ የእነዚያ በአንተ ከሁሉም በላይ ክብር የተመላና ከሁሉም በላይ ታላቅ የሆነ ህልውና እናምንም ያሉት ሰዎች የሚያቀርቡአቸው ሃሳቦች ከአንተ ሊከለክሉአቸው በማይችሉበት ሁኔታ በአንተ ቅርበት ሰማይ ውስጥ እንዲበሩ አድርጋቸው፤
አቤቱ አንተ የተፈጠሩትን ነገሮች ሁሉ በትዕዛዝህ ኃይል ወደ መኖር ያመጣህ ጌታ ሆይ ክብር ለአንተ ይሁን! ጌታ ሆይ! እነዚያን ከአንተ በስተቀር ሌላውን የተውትን እርዳቸው ፣ታላቅ ድልም አቀዳጃቸው፤ ጌታ ሆይ ፣አገልጋዮችህን ለመርዳት ለማበረታትና ለማጠናከር ስኬታማም እንዲሆኑ ለማስቻል፣ ለመደገፍ ገናናነትን ክብርንና ከፍተኝነትን ለማጎናፀፍ፣ ለማበልፀግና በድንቅ ድልም አሸናፊዎች እንዲሆኑ ለማድረግ በሰማይና በምድር በመከላከላቸውም ሁሉ የሚገኙትን የመላእክት ሠራዊት ላክላቸው፤
አንተ የእነርሱ ጌታ፣ የሰማያትና የምድር ጌታ የሁሉ ዓለማት ጌታ ነህ፤ ጌታ ሆይ፣ በእነዚህ አገልጋዮችህ ኃይል፣ ይህን እምነት አጠናክረው በዓለም ህዝቦች ሁሉ ላይ የበላይነትን እንዲያገኙ አድርጋቸው፣ እነርሱ በእውነቱ ከአንተ በስተቀር ከማንኛውም ነገር ራሳቸውን ያለቀቁ አገልጋዮችህ ናቸው፤ አንተ በእርግጥ የእውነተኛ እማኞች መከታ ነህና፡፡
ጌታ ሆይ፣ በእነርሱ ለዚህ ለማይደፈረው እምነት ታማኝ መሆን አማካይነት፣ ልቦቻቸው በሰማያትና በምድር ከመካከላቸውም ከሚገኘው ከማንኛውም ነገር የበለጠ እየጠነከሩ እንዲሄዱ ፈቃድህ ይሁን፣ ጌታ ሆይ በሁሉም የሰው ዘር የተኮረ እይታ ፊት ኃይልህን ያሳዩ ዘንድ እጆቻቸውን በድንቅ ኃይልህ ምልክቶች አበርታ፤
ጌታ ሆይ ! በመንገድህ ሰማዕትነትን ስለፈለጉ ለታጋሽ አገልጋዮችህ በቀናትህ ተገቢ ድል በመፍቀድ አሸናፊዎች አድርጋቸው፡፡ ያንን ለዐዕምሮዎቻቸው መጽናናትን የሚያመጣውን ውስጣዊ ሕያውነቶቻቸው ሐሴት እንዲያደርጉ የሚያደርገውን፣ለልቦቻቸው እርግጠኝነትን ለአካሎቻቸውም መረጋጋትን የሚሰጠውንና ነፍሶቻቸውን ወደ አምላክ፣ ከሁሉም በላይ ወደተከበረው ዘንድ ለመውጣት፣ ወደ ላቀው ገነትና አንተ ለእውነተኛ የዕውቀትና የመልካም ተግባር ሰዎች ወደ አዘጋጀሃቸው የክብር አካባቢዎች ለመድረስ የሚያስችላቸውን ላክላቸው፤ በእውነቱ አንተ ሁሉን ነገሮች ታውቃለህ፤ እኛ ግን አገልጋዮችህ፣ ምርኮኞችህ ባሮችህና ምስኪኖችህ ነን፡፡ እግዚአብሄር ጌታችን ሆይ ከአንተ በቀር ሌላ ጌታ አንጠራም፣ አቤቱ አንተ ለዚህ ዓለምና ለሚቀጥለው የምህረት አምላክ የሆንክ ሆይ፣ ከአንተ በቀር ከሌላ ከማንም ቡራኬዎችን ወይም ጸጋን አንማፀንም የአንተ መላው ህያውነት የሀብት፣የነፃነት የክብር የግርማና የወሰን አልባ ፀጋ ምሳሌ ሲሆን፣ እኛ ግን የድህነት፣የኢምንትነት፣ የረዳት ቢስነትና የጥፋት መገለጫዎች ነን፡፡
ጌታ ሆይ፣ካሳችንን ከዚህና ከሚቀጥለው ዓለም መልካም ነገሮች ከሰማይ ጀምሮ ከዚያ በታች እስካለችው ምድር ከተዘረጉትም ብዙና ልዩ ልዩ ፀጋዎች ከአንተ መሠጠቱ በጣም ወደሚገባው ለውጠው፡፡
በእውነቱ አንተ ጌታችንና የሁሉ ነገሮች ጌታ ነህ፤ ከአንተ ለሆኑት ነገሮች በመጓተት፣ራሳችንን አሳልፈን ለእጅህ እንሰጣለን፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ሆይ! ከሁሉም በላይ ከፍተኛ በሆነው ተራራ ጫፍ ላይ ባለው ቅዱስ ዛፍ፣ በዚያ ምሥራቃዊም ምዕራባዊም ባልሆነ ዛፍ ውስጥ ያንን ነበልባሉ ወደ ሰማይ ሠራዊት እስኪያደርግ ድረስ የተንበለበለውን እሳት፣ ከዚያም ነበልባል፣ እነዚያ እውነታዎች የመርሐን ብርሃን የጨበጡትና በእውነቱ እኛ በደብረ ሲና ተራራ ዳገት ላይ እሳት አየን በማለት የጮሁለትን የመለኮታዊ ፍቅር እሳት ስላቀጣጠልክ ምስጋና ለአንተ ይሁን፤
እግዚአብሔር አምላኬ ሆይ! ከፍተኛ ነበልባሉ መላዋን ምድር ለማንቀሳቀስ እስኪችል ድረስ፣ ቀን በቀን በተተካ ቁጥር ይህ እሳት እየጨመረ እንዲሄድ አድርግ፤ አቤቱ አንተ ጌታዬ ሆይ! የፍቅርህ ብርሃን በእያንዳንዱ ልብ ውስጥ እንዲያበራ አድርግ፤ የዕውቀትህን መንፈስ በሰዎች ነፋሶች ውስጥ ተንፍስ፤ በአንድነትህ ጥቅሶች ልቦቻቸውን አስደስት፤ እነዚያን በመቃብሮቻቸው ውስጥ የሚኖሩትን ወደ ህይወት ጥራቸው፤ ትዕቢተኞችን አስጠንቀቅ፤ ደስታ መላዋን ምድር እንዲያቅፍ አድርግ፣ የጠሩ ውሃዎችን ላክልን፣ በግልጽ ውበቶች በተመላውም ጉባኤ ላይ፣ ያንን ከካምፉር ምንጭ የተበረዘውን፤ ጽዋ አዙርላቸው፤
………
1. ቁርአን 24፣35
2. ኡርአን፤ 28፣29
3. ቁርአን 76፣5
በእውነቱ አንተ ሰጪው ይቅር ባዩ፤ ምንጊዜም ለጋሱ ነህ፤ በእርግጥም አንተ መሐሪው ሩኅሩኁ ነህ፡፡
እርሱ አምላክ ነው!
አቤቱ አንተ እጅግ ተወዳጄ የሆንክ ጌታ አምላክ ሆይ! እነዚህ ድምጽህን የሰሙ፣ ለቃልህ ጆሮዎቸቸውን ያቀኑ ወደ ጥሪህም ያዳመጡ አገልጋዮችህ ናቸው፡፡ በአንተ አምነዋል የአንተን ድንቅ ስራዎች አይተዋል፣ የማስረጃህን ትክክልነት ተቀብለዋ፤ ስለማረጋገጫህም መስክረዋል፤ በመንገዶችህም ተራምደዋል፤ መርሆህን ተከትለዋል፤ አንተን ምስጢራት ተረድተዋል፣ የመጽሐፍህን ድብቅ ይዘት፣ የብራናህን ጥቅሶች የመልእክቶችህንና የጽላቶችህንም አስደሳች ዜናዎች ተገንዝበዋል፡፡ በልብስህ ጠርዝ ላይ ተንጠላጥለዋል፡፡ የብርሃንህንና የታላቅነትህንም ካባ አጥብቀው ይዘዋል፡፡ እርምጃዎቻቸው በቃ- ኪዳንህ መንገድ ተጠናክረዋል፡፡ ልቦቻቸውም ለአዲሱ ሥርዓትህ ጽኑዎች ሆነዋል፡፡ ጌታ ሆይ! የመለኮታዊ መስብህን ነበልባል በልቦቻቸው ውስጥ አቀጣጥል፤ የፍቅርና የማስተዋል ወፍም ከልቦቻቸው ውስጥ እንድትዘምር ፈቃድህ ይሁን፣ አሳማኝ ምልክቶች አንፀባራቂ ሰንደቅ ዓላማዎች እንደ ቃልህም ፍጹማን እንዲሆኑ አድርጋቸው፡፡ በእነርሱ አማካይነት እምነትህ እንዲከበር የአንተ ኣርማዎች እንዲዘረጉ ድንቅ ስራዎችህም በስፋትና በጥልቀት እንዲሰራጩ፣ ቃልህም ድል እንዲነሳ አድርግ የተወዳጆችህንም ወገቦች አበርታ፤ ስምህን እንዲያወድሱ አንበቶቻቸውን አፍታታ፣የአንተንም ቅዱስ ፈቃና ፍላጎት ለመፈፀም እንዲችሉ አነቃቃቸው፤ ፊቶቻቸውን በቅዱስነት መንግስትህ ውስጥ አብራ እምነትህ ድልን እንዲጎናፀፍ ለማድረግ እንዲነሱ በመርዳት ደስታቸውን ፍጹም አድርግላቸው፡፡
ጌታ ሆይ! እኛ ደካሞች ነን፣ የቅዱስነትህን መዓዛዎች ለማሰራጨት እንድንችል አበርታን፣ ምስኪኖች ነን፤ በመለኮታዊ አንድነትህ ግምጃ-ቤቶች ውስጥ ከሚገኙት ሀብቶችህ አበልጽገን፣ የተራቆትን ነን፣ የፀጋህን ካባ ሀብቶችህ አበልጽገን፣ የተራቆትን ነን፤ የፀጋህን ካባ አልብሰን፣ኃጢአተኞች ነን፤ ኃጢአታችንን በፀጋህ በችሮታህና በይቅር ባይነትህ ይቅር በለን፡፡ በእውነቱ፣ አንተ ረዳቱ አጋዡ ፀጋ የተመላው ኃያሉ ፣ኃይል የተመላው ነህና፤
የእርሱ፣ የንዑሱ ክብር በእነዚያ ጥብቅና ፅኑዎች በሆኑት ላይ ይረፍ፡፡
- Bahá'u'lláh