Return to BahaiPrayers.net
Facebook
Infants
ጌታ አምላኬ ሆይ፡ ምስጋና ለአንተ ይሁን ይህ ህፃን በፀጋህ የፍቅራዊ ምሕረትህንና ርኅራኁ የተመላበት የአምላካዊ ጥበቃህን ጡት እንዲጠባ የመንግስተ ሰማያዊ ዛፎችህንም ፍሬዎች እንዲመገብ ፈቃድህ ይሁን፡፡ አንተ ራስህ በላቀው ፈቃድህና ሥልጣንህ ኃይል ስለፈጠርከውና ወደ መኖር ስለጠራኽው ለአንተ እንጂ ለሌላ ለማንም እንክብካቤ እንዲተው አታድርገው ከአንተ ከፍፁም ኃያሉ ከሁሉን አዋቂው በስተቀር ሌላ አምላክ የለም፡፡
አቤቱ አንተ ከሁሉም በላይ ተወዳጄ ሆይ፤ የተወደስክ ነህ ከሁሉ የላቀ በረከትህን ጣፋጭ ሽታና የቅዱስ ስጦታዎችህን መዓዛዎች በላዩ አርብብበት፡፡ ከዚያም አቤቱ አንተ ስሞችና የባህርያት መንግስትን በመዳፈህ ውስጥ ይዘህ ያለኽው ሆይ ከሁሉም በላይ በተከበረው ስምህ ጥላ ሥር መጠለያ ለመፈለግ አስችለው፤ በእውነቱ አንተ የፈቀድከውን ለማድረግ የማይሳንህ ነህ፤ በእርግጥም አንተ ኃያሉ የተከበረው ዘለዓለም ይቅር ባዩ ፀጋ የተመላው ለጋሱ መሐሪው ነህና፤
ጌታ አምላኬ ሆይ ይህ አንተ በማይሻረው ትዕዛዝህ መልእክቶችና በፈቃድህ መፃሕፍት ውስጥ የተከበረ ደረጃ እንዲኖራቸው ከፈቀድህላቸው አገልጋዮችህ መካከል ከአንዱ አብራክ የተገኘ ልጅ ነው፡፡
ይህ ልጅ በአገልጋዮችህ መካከል በሳል ነፍስ እንዲሆን ፈቃድህ ይሆን ዘንድ፣ እያንዳንዱን ሰው ወደ ፍላጎቱ ዓላማ ለመድረስ በአስቻልክበት ስምህ እማፀንሃለሁ፣ በስምህ ኃይል አማካይነት እንዲያበራ አድርገው፣የአንተን ምስጋና ለመናገር ፊቱን ወደ አንተ ለመመለስና ወደ አንተ ለመቅረብ አስችለው በእውነቱ ከእምቅድመ ዓለም ጀምሮ እንደፈቃድህ ለማድረግ ኃይል የነበረህ፣እስከ ዘለዓለምም የፈቀድኽውን ለማድረግ የማይሳንህ ሆነህ የምትኖረው አንተ ነህ፤ ከአንተ ከተከበረው ግርማ ሞገስ ከተመላው ከድል አድራጊው ከኃያሉ፣ ከሁሉን አስገዳጁ በቀር ሌላ አምላክ የለም፡፡
ጌታዬ ሆይ ጌታዬ ሆይ በለጋነት ዕድሜ ያለሁ ሕፃን ነኝ፡፡ ከምሕረትህ ጡት ወተት መግበኝ፣ በፍቅርህ እቅፍ ውስጥ አሰልጥነኝ፣ በአንተ መርሖ ትምህርት ቤት አስተምረኝ፣ በበረከትህ ጥላ ሥር አጎልምሰኝ፤ ከጨለማ አውጣኝ ደማቅ ብርሃን አድርገኝ ከደስታ ማጣት አድነኝ፣የጽጌረዳ አትክልት ሥፍራ አበባ አድርገኝ የደጀሰላምህ አገልጋይ እንድሆን አድርገኝ የፃድቃንንም ዝንባሌና ጠባይ አጎናጽፈኝ ፣ለሰው ዘር ዓለም የበረከት መንስኤ አድርገኝ፣ በራሴም ላይ የዘለዓለም ህይወት አክሊል ድፋልኝ!
በእውነቱ አንተ ኃይል የተመላው ኃያሉ፣ ሁሉን የሚያው ሰሚው ነህና፤
አምላኬ ሆይ ምራኝ፣ ጠብቀኝ ብሩህ መብራትና አንፀባራቂ ኮከብ አድርገኝ፣ አንተ ኃያሉና ኃይል የተመላው ነህና፤
አምላክ ሆይ እነዚህን ህፃናት አስተምራቸው እነዚህ ህፃናት የአትክልት ሥፍራህ ተክሎች የመስክህ አበባዎች አትክልት ቦታህ ፅጌረዳዎች ናቸው፡፡ ዝናብህ እንዲዘንብላቸው የአውነት ፀሐይ ከፍቅርህ ጋር እንዲበራላቸው አድርግ፣ ይሠለጥኑ ያድጉና ይዳብሩ፣ በከፍተኛ ውበትም ይታዩ ዘንድ፣
የአንተ ልዝብ ነፋስ እንዲያድሳቸው ፈቃድህ ይሁን አንተ ሰጪው ነህ፡፡ አንተ ሩኅሩኁ ነህ፡፡
አምላክ ሆይ ይህን ጨቅላ ህፃን በፍቅርህ ጉያ ተንከባከበው ከመለኮታዊ ጠባቂነትህም ጡት ወተት ለግሰው፡፡ ይህን ለጋ ቡቃያ በፍቅርህ የጽጌረዳ አትክልት ሥፍራ ውስጥ ኮትኩተህ አሳድገው፤ ከፀጋህም በሚወርደው ዝናብ እንዲያድግ እርዳው፡፡ የመንግስተ ሰማይ ልጅ አድርገው ወደ መንግስተ ሰማያዊው ዓለምህም ምራው ፡፡ አንተ ኃይል የተመላህና ደግ ነህ፣ አንተ ሰጪው ቸሩ፣የተትረፈረፈ በረከት ባለቤት ነህና፤
- Bahá'u'lláh